Numbers 18

የካህናትና የሌዋውያን ተግባር

1 እግዚአብሔር (ያህዌ) አሮንን እንዲህ አለው፤ “መቅደሱን በተመለከተ ስለሚፈጸም በደል አንተ፣ ልጆችህና የአባትህ ቤተ ሰቦች ኀላፊነቱን ትሸከማላችሁ፤ ክህነቱን በተመለከተ ስለሚፈጸም በደል ግን ኀላፊነቱ የሚወድቀው በአንተና በልጆችህ ላይ ብቻ ነው። 2አንተና ልጆችህ በምስክሩ ድንኳን ፊት በምታገለግሉበት ጊዜ አብረዋችሁ እንዲሆኑና እንዲረዷችሁ ከአባትህ ነገድ ሌዋውያንን አምጣቸው። 3እነርሱም በአንተ ኀላፊነት ሥር ሆነው የድንኳኑን አገልግሎት በሙሉ ያከናውኑ፤ ይሁን እንጂ ወደ መቅደሱ ዕቃዎችም ሆነ ወደ መሠዊያው አይጠጉ፤ ከተጠጉ ግን እነርሱም አንተም ትሞታላችሁ። 4እነርሱም የመገናኛውን ድንኳን ለመንከባከብ ማለትም በድንኳኑ ውስጥ የሚሠራውን ሥራ ሁሉ ኀላፊነት በመውሰድ አብረዋችሁ ይሁኑ፤ ከዚህ በተረፈ ግን እናንተ ወዳላችሁበት ማንም ሰው አይጠጋ።

5“በእስራኤላውያን ላይ ዳግም ቍጣ እንዳይደርስባቸው የመቅደሱና የመሠዊያው እንክብካቤ ኀላፊነት የሚመለከተው እናንተን ይሆናል። 6ከእስራኤላውያን መካከል ወገኖቻችሁን ሌዋውያንን ለእናንተ ስጦታ አድርጌ እኔ ራሴ መርጫቸዋለሁ፤ በመገናኛው ድንኳን ውስጥ የሚከናወነውን ሥራ ሁሉ እንዲሠሩ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የተሰጡ ናቸው። 7ይሁን እንጂ በመሠዊያው ላይ የሚደረገውንና በመጋረጃ ውስጥ ያለውን ማንኛውንም የክህነት አገልግሎት የምትፈጽሙት አንተና ልጆችህ ብቻ ናችሁ፤ የክህነቱን አገልግሎት ስጦታ አድርጌ ሰጥቻችኋለሁ። ከእናንተ በስተቀር ወደ መቅደሱ የሚጠጋ ቢኖር ግን ይገደል።”

ለካህናትና ለሌዋውያን የሚሰጡ መባዎች

8ከዚያም እግዚአብሔር (ያህዌ) አሮንን እንዲህ አለው፤ “ለእኔ በሚቀርበው መባ ላይ ኀላፊነትን የሰጠሁህ እኔው ራሴ ነኝ፤ እስራኤላውያን የሚያቀርቡልኝም የተቀደሰ መባ ሁሉ ለአንተና ለልጆችህ መደበኛ ድርሻችሁ እንዲሆን ሰጥቻችኋለሁ። 9ለእኔ ከሚቀርብልኝ እጅግ ከተቀደሰው መባ ሁሉ፣ በእሳት የማይቃጠለው የራስህ ድርሻ ይሆናል፤ እጅግ የተቀደሰ አድርገው ከሚያመጡልኝ ስጦታ ከእህል ቍርባንም ሆነ ከኀጢአት ወይም ከበደል መሥዋዕት የሚነሣው ሁሉ የአንተና የልጆችህ ድርሻ ነው። 10እጅግ ቅዱስ መሆኑን በማሰብ በተቀደሰ ስፍራ ብላው፤ እያንዳንዱም ወንድ ከዚሁ ይብላ፤ ይህ ለአንተም የተቀደሰ ነው።

11“እስራኤላውያን ከሚያቀርቡት ስጦታ፣ ከሚወዘወዘው ቍርባን ተለይቶ የሚቀመጠው ስጦታ ሁሉ የአንተ ይሁን። ይህንም ለአንተ፣ ለወንድና ለሴት ልጆችህ መደበኛ ድርሻ አድርጌ ሰጥቻችኋለሁ። ከቤተ ሰዎችህ በሥርዐቱ መሠረት የነጻ ማንኛውም ሰው ከዚሁ መብላት ይችላል።

12“እስራኤላውያን የመከር በኵራት አድርገው ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የሚሰጡትን ምርጥ የወይራ ዘይት በሙሉ፣ ምርጥ የሆነውን አዲስ የወይን ጠጅና እህል ሁሉ ለእናንተ ሰጥቻችኋለሁ። 13ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የሚያመጡት የምድሪቱ በኵር ፍሬ ሁሉ የአንተ ይሆናል። ከቤተ ሰዎችህ በሥርዐቱ መሠረት ንጹሕ የሆነ ማንኛውም ሰው ይህን መብላት ይችላል።

14ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ፈጽሞ የተሰጠ
የዕብራይስጡ ትርጕም አንድን ነገር ወይም አንድን ሰው በማይለወጥ ውሳኔ ለእግዚአብሔር መስጠትን ያመለክታል።
በእስራኤል ያለ ማንኛውም ነገር ሁሉ የአንተ ነው።
15ማሕፀን የሚከፍትና ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የተሰጠ ሰውም ሆነ እንስሳ የአንተ ነው፤ ነገር ግን ማንኛውም በኵር ሆኖ የተወለደውን ወንድ ልጅና ንጹሕ ካልሆነ እንስሳ በኵር ሆኖ የተወለደውን ተባዕት ሁሉ ዋጀው። 16እነዚህም አንድ ወር ሲሆናቸው ሃያ ጌራ በሚመዝነው በቤተ መቅደሱ ሰቅል
አምሳ አምስት ግራም ያህል ነው።
ልክ፣ በተወሰነው በመዋጃው ዋጋ በአምስት ሰቅል ጥሬ ብር ትዋጀዋለህ።

17“የተቀደሱ ስለሆኑ የበሬ፣ የበግ ወይም የፍየል በኵር የሆኑትን አትዋጃቸውም፤ ደማቸውን በመሠዊያው ላይ ትረጨዋለህ፤ ሥባቸውንም ሽታው እግዚአብሔርን (ያህዌ) ደስ የሚያሰኝ እንዲሆን በእሳት የሚቀርብ መሥዋዕት አድርገህ ታቃጥለዋለህ። 18የሚወዘወዘው ቍርባን ፍርምባና የቀኙ ወርች የአንተ እንደ ሆነ ሁሉ የእነዚህም ሥጋ የአንተ ይሆናል። 19እስራኤላውያን ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ከሚያቀርቡት ከተቀደሰ ቍርባን የሚለየው ሁሉ ለአንተ፣ ለወንድና ለሴት ልጆችህ መደበኛ ድርሻ አድርጌ ሰጥቻችኋለሁ፤ ይህም በእግዚአብሔር (ያህዌ) ፊት ለአንተና ለዘሮችህ ዘላለማዊ የጨው ኪዳን ነው።” 20እግዚአብሔር (ያህዌ) አሮንን እንዲህ አለው፤ “ከምድራቸው የምትካፈለው ርስት፣ ከእነርሱም የምታገኘው ድርሻ የለህም፤ በእስራኤላውያን መካከል ድርሻህና ርስትህ እኔ ነኝ።

21“በመገናኛው ድንኳን በሚያገለግሉበት ጊዜ ለሚሠሩት ሥራ ደመወዝ እንዲሆናቸው ከእስራኤል የሚወጣውን ዐሥራት ሁሉ ለሌዋውያን ርስት አድርጌ ሰጥቻቸዋለሁ። 22አድራጎቱ ኀጢአት ስለሆነ ሞት እንዳያስከትልባቸው ከእንግዲህ ወዲያ እስራኤላውያን ወደ መገናኛው ድንኳን አይጠጉ። 23በመገናኛው ድንኳን የሚከናወነውን ሥራ የሚሠሩት ሌዋውያን ናቸው፤ በዚያም ለሚፈጸመው በደል ኀላፊነቱን ይሸከማሉ። ይህም ለሚመጡት ትውልዶች የዘላለም ሥርዐት ነው፤ ሌዋውያን በእስራኤላውያን መካከል ርስት አይሰጣቸውም። 24በዚህ ፈንታም እስራኤላውያን መባ አድርገው ለእግዚአብሔር (ያህዌ) የሚያቀርቡትን ዐሥራት ለሌዋውያን ርስት አድርጌ ሰጥቻቸዋለሁ፤ እኔም እነርሱን በተመለከተ፣ ‘በእስራኤላውያን መካከል ርስት አይኖራቸውም’ ያልሁት በዚሁ ምክንያት ነው።”

25 እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤ 26“ሌዋውያንን ተናገራቸው፤ እንዲህም በላቸው፤ ‘ርስት አድርጌ የምሰጣችሁን ዐሥራት ከእስራኤላውያን በምትቀበሉበት ጊዜ፣ እናንተም ካገኛችሁት ላይ አንድ ዐሥረኛ በማውጣት ለእግዚአብሔር (ያህዌ) መባ አድጋችሁ ታቀርባላችሁ። 27ቍርባናችሁም ከዐውድማ እንደ ገባ እህል ወይም ከመጭመቂያ እንደ ወጣ ወይን ሆኖ ይቈጠርላችኋል። 28እናንተም ከእስራኤላውያን ላይ ከምትቀበሉት ዐሥራት ሁሉ በዚሁ ዐይነት ለእግዚአብሔር (ያህዌ) መባ ታቀርባላችሁ፤ ከዚሁም የእግዚአብሔር (ያህዌ) ድርሻ የሆነውን ዐሥራት ለካህኑ ለአሮን ትሰጣላችሁ። 29ከምትቀበሉት ሁሉ ምርጥና እጅግ የተቀደሰውን ክፍል የእግዚአብሔር (ያህዌ) ድርሻ አድርጋችሁ ታቀርባላችሁ።’

30“ሌዋውያንን እንዲህ በላቸው፤ ‘ምርጥ የሆነውን ክፍል በምታቀርቡበት ጊዜ፣ እንደ ዐውድማ ምርት ወይም እንደ ወይን መጭመቂያ ውጤት ሆኖ ይቈጠርላችኋል። 31የቀረው ግን በመገናኛው ድንኳን ለሰጣችሁት አገልግሎት ደመወዛችሁ ስለሆነ፣ እናንተና ቤተ ሰዎቻችሁ በየትኛውም ስፍራ ልትበሉት ትችላላችሁ። 32የተመረጠውን ክፍል ካቀረባችሁ በዚህ በደለኞች አትሆኑም፤ ደግሞም የተቀደሰውን የእስራኤላውያንን መባ አታረክሱም፤ አትሞቱምም።’ ”

Copyright information for AmhNASV